28/07/2025
🕊
የትግራይ ክልል አመራሮችና ፓለቲከኞች አሁንም በፍፁም ትዕግስትና ቻይነት የተጀመረውን ሰላም እንዲያፀኑና ከዳር እንዲያደርሱ ተማፅኖ ቀረበ።
ተማፅኖ ያቀረቡት ከ12 ክልሎችና የከተማ አስተዳደሮች የተውጣጡ የሃይማኖት አባቶችና የአገር ሽማግሌዎች ናቸው።
ቁጥራቸው 50 የሆኑት መላ የኢትዮጵያ ክልሎችና የከተማ አስተዳደሮች የወከሉ የሰላም ልኡካን ዛሬ ሀምሌ 21/2017 ዓ.ም ጠዋት መቐለ አሉላ አባነጋ አውሮፕላን ማረፍያ ሲደርሱ የጊዚያዊ አስተዳደሩ ከፍተኛ አመራሮች ፣ የሃይማኖት አባቶች ፣ የአገር ሽማግሌዎች ፣ ባለሃብቶችና ታዋቂ ሰዎች አቀባበል አድርገውላቸዋል።
ከአውሮፕላን ማረፍያ ውይይቱ ወደ ሚካሄድበት ቦታ ያቀኑት የሰላም ልኡካኑ ፕሬዜዳንት ሌ/ጄነራል ታደሰ ወረደና እና ካቢኔያቸው በተገኙበት በየእምነታቸው ፀሎት አድርሰዋል።
የክልሉ አመራሮችና ፓለቲከኞችም ለተሻለ ሰላምና አገራዊ መረጋጋት አሁንም በፍፁም ትዕግስትና ቻይነት ተጨማሪ ግጭት እንዲያስቀሩ አባታዊና ሃይማኖታዊ ምክርና ተማፅኖ ቀርበውላቸዋል።
የሰላም ልኡካኑ ከጦርነቱ በፊት ወደ ትግራይ ተመላልሰው ያደረጉት ጥረት ግጭቱ ማስቀረት ባለመቻሉ በቁጭት አስታውሰው ከፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነት በኃላ ለሦሥተኛ ጊዜ መምጣታቸውና የሰላም ጥረታቸው ሳይታክቱ እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።
" የጀመረው ሰላም እንዲፀና ፤ ዳግም ጦርነት እንዳይቀሰቀስ ከመስራትና ከመጣር የበለጠ ሃይማኖታዊና አባታዊ ተልእኮ የለንም ለዚህም የሚከፈለውን ሁሉም ዓይነት መስዋእትነት እንከፍላለን " ብለዋል።
የሰላም ልኡካኑ ከትግራይ ጊዚያዊ አስተዳደርና ካቢኔያቸው ፣ የፐብሊክ ዲፕሎማሲ አባላት፣ የተፎካካሪ የፓለቲካ ፓርቲ አመራሮችና ስቪክ ማህበራት እንደሚወያዩ ከወጣው መርሀ ግብር ሐመረዳት ተችሏል።