29/07/2026
ሣምንታዊ መልዕክት!
የፓርቲያችን አመራሮችና አባላት የሕዝብ አገልጋይነታቸውን በተጨባጭ ውጤት ማረጋገጥ አለባቸው።
የ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸም ግምገማና የ2019 በጀት ዓመት መሪ ዕቅድ የውይይት መድረክ ባሳለፍነው ሳምንት ከሀምሌ 13 እስከ 15/2018 ዓ.ም ተከታታይ ቀናት በስፋት ተካሂዷል። በዚህ መድረክ የአፈጻጸም ውጤቶችን በጥልቀት ተገምግሟል፤ በስራ ዕድል ፈጠራ፣ በኑሮ ውድነት ቅነሳና ገበያ ማረጋጋት ዙሪያ በንቅናቄ የተከናወኑ አበይት ተግባራት ውይይት ተደርጎባቸዋል፤ በቀጣይም የሕዝቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የትኩረት አቅጣጫዎችም ተቀምጠዋል።
2018 በጀት ዓመት ኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ፣ ፍትሃዊ፣ ነፃና ተዓማኒ የሆነውን 7ኛውን ጠቅላላ ምርጫ ያካሄደችበት ነው። ፓርቲያችን ብልፅግና ይህ ታሪካዊ ስኬት በዋናነት በመምራት አንፀባራቂ ድል ያስመዘገበ ሲሆን በመራጩ ህዝብ ዘንድ ባገኘው ቅቡልነትም ሀገርንና ህዝብን ለቀጣይ 5 ዓመታት የመምራት እድል አግኝቷል።
2019 በጀት ዓመት ደግሞ መራጩ ህዝብ የሰጠውን ታሪካዊ ኃላፊነት መወጣት የምንጀምርበት፤ ህዝቡ በተለያዩ ጊዜያት የሚያነሳውን የልማት፣ የመልካም አስተዳደርና ሌሎች ጥያቄዎችን ለመፍታት በትጋት የምንሰራበት እንዲሁም ፓርቲያችን የጀመራቸውን የልማት ኢኒሼቲቮች ስኬት በይበልጥ የምናረጋግጥበትና የዜጎችን ተጠቃሚነት የምናረጋግጥበት ነው። ለዚህ ስኬት ደግሞ የላቀ የአመራርና አባላት ቁርጠኝነት፤ የህዝብ የነቃ ተሳትፎ የሚጠይቅ በመሆኑ ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ ይገባል።
በ2018 በጀት ዓመት በስራ ዕድል ፈጠራ፣ በገበያ ማረጋጋትና በኑሮ ውድነት ቅነሳ ዙሪያ የተከናወኑ ስራዎች የፓርቲያችን አቅጣጫ ትክክለኛ መሆኑን ያረጋገጡ ናቸው። በሁሉም ክልሎች በተፈጠሩ የስራ ዕድሎች፣ በምርት አቅርቦት መጨመር፣ በገበያ ማረጋጋትና በሕዝቡ የኑሮ ሁኔታ ላይ የተመዘገቡ መሻሻሎች የፓርቲያችን የሕዝብ ተጠቃሚነትን ያማከለ ፖለቲካ ውጤቶች ናቸው።
ይሁን እንጂ የተገኙት ውጤቶች የጉዟችን መጨረሻ ሳይሆኑ የቀጣይ ከፍተኛ ስኬት መነሻዎች ናቸው። ከሀገራችን አቅምና ከሕዝባችን ፍላጎት አንጻር ገና ብዙ ሊሰራ የሚገባ ስራ አለ። በመሆኑም በየደረጃው ያለው አመራር የሕዝብን ችግር ዋና የስራ አጀንዳው በማድረግ የተጀመሩ ለውጦችን ወደ ከፍተኛ ውጤት ማሸጋገር አለበት።
የስራ ዕድል ፈጠራና የኑሮ ውድነት ቅነሳ የአንድ ተቋም ወይም የአንድ ዘርፍ ብቻ ኃላፊነት አይደሉም። እስከ ቀበሌ ድረስ በሁሉም የፓርቲ አደረጃጀቶች፣ በመንግሥት ተቋማትና በሕዝቡ የተቀናጀ እንቅስቃሴ ሲኖር ብቻ ዘላቂ ውጤት ማስመዝገብ ይቻላል።
በቀጣይ የእያንዳንዱን አካባቢ እምቅ አቅም በአግባቡ በመጠቀም፣ የሕዝብ ተሳትፎንና ባለቤትነትን በማጠናከር፣ ከአሰራር፣ ከአመለካከትና ከአስተሳሰብ ጋር የተያያዙ ማነቆዎችን በመፍታት የብልፅግናን ጉዞ ወደ ከፍተኛ ደረጃ ማሸጋገር አለብን።
በተለይም የፓርቲያችን አመራሮችና አባላት የሕዝብ አገልጋይነታቸውን በተጨባጭ ውጤት ማረጋገጥ አለባቸው። ሕዝባችንም በልማት ስራዎች የጀመረውን ንቁ ተሳትፎና ባለቤትነት በቀጣይነት በማጠናከር የሀገራችንን የብልፅግና ጉዞ የበለጠ እንዲፋጠን የበኩሉን ሚና መወጣት ይጠበቅበታል።
በ2019 በጀት ዓመት የተቀመጡትን ዕቅዶች ከግብ ለማድረስ በአንድነት፣ በቅንጅት፣ በተጠያቂነትና በውጤት ተኮር አሰራር መስራት ይገባል። የሕዝባችንን ተስፋ ወደ ተጨባጭ ውጤት፣ የሀገራችንን አቅም ወደ ሁለንተናዊ ብልፅግና ለመቀየር ሁላችንም በላቀ ቁርጠኝነት ልንረባረብ ይገባል።
ብልፅግና ፓርቲ
ሀምሌ 20/2018 ዓ.ም
አዲስ አበባ