06/04/2026
ጁን 4 - 2026 (ግንቦት 27/2018) - ሮም ጣልያን
የ2026 ዳይመንድ ሊግ አራተኛ መዳረሻ በሆነው የሮሙ ጎልደንጋላ ፒዬትሮ ሜኒአ የሴቶች 5000ሜ. ውድድር ኢትዮጵያውያን አትሌቶች የመጀመሪያዎቹን ሰባት ደረጃዎች በመቆጣጠር ጨርሰዋል፡፡ ልቅና አምባው የግሏን ምርጥ ከአምስት ሰከንድ በላይ ባሻሻለችበት እና የወቅቱ የርቀቱ ፈጣን በሆነ 14:18.41 ሰዓት ስታሸንፍ አለሺኝ ባወቀ (14:18.54 PB) እና ፍሬወይኒ ሀይሉ (14:18.94 PB) ሁለተኛ እና ሶስተኛ ሆነው ጨርሰዋል፡፡
ውድድሩን ካጠናቀቁት አስራ ስምንት አትሌቶች አስራ ሁለቱ የግል ምርጥ ሰዓታቻውን ያሻሻሉበት ይህ ፉክክር የባህሬን እና ፈረንሳይ ብሔራዊ ክብረወሰኖች የተሰበሩበትም ነው፡፡
የውድድሩ አሸናፊ የሆነችው ልቅና አምባው ካስመዘገበችው ድል በኋላ ለውድድሩ አዘጋጆች በሰጠችው አስተያየት ‹‹በዳይመንድ ሊግ ውድድር ላይ የመጀመሪያ ድሌን በማስመዝገቤ በጣም ደስ ብሎኛል፡፡ (የእጅ ሰዓቷን ተመልክታ) ኦ እንደዚህ አይነት ሰዓት እንደሮጥኩ አላውቅም ነበር፡፡ በስታድየም ውስጥ የነበሩት ተመልካቾች በጣም ጥሩ ናቸው፡፡ የሞራል ድጋፋቸውም ከፍተኛ ነበር፡፡ በጣም ጠንካራ ስራዎችን ሰርቻለሁ በአጨራረስ የፍጥነት ሩጫዬ ላይ ጭምር፡፡ ለግዜው አምስት ሺህ ሜትር መሮጤን እቀጥላለሁ ወደፊት ምናልባትም በአስር ሺህ ሜትርም እወዳደር ይሆናል›› ብላለች፡፡
በሮም ዳይመንድ ሊግ የዳይመንድ ሊጉ የነጥብ ፉክክር አካል ባልነበረው የሴቶች 1500ሜ. ውድድር የግሬት ብሪቴይኗ ጆርጂያ ሀንተር ቤል (3:58.63 SB) ስታሸንፍ ብቸኛዋ ኢትዮጵያዊት ተወዳዳሪ የነበረችው ሐረገወይን ካላዩ 4:03.43 በሆነ ሰዓት ዘጠነኛ ሆና ጨርሳለች፡፡