12/06/2024
የኦሊምፒክ ኮሚቴው ሚስጥራዊ ጉባኤ...
🔵አስር ወር የሚቀራቸው ዶ/ር አሸብር ለ3ኛ ጊዜ ተመርጠዋል
🔵 ሀይሌ፣ ደራርቱና ብርሀኔ ምክትል ሆነዋል
🔵 በምርጫው የሀገሪቱ ህጎች ተጥሰዋል
ትናንት ሰኔ 4/2016 ወሎ ሰፈር በሚገኘው የኢትዮጵያ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ፅህፈት ቤት ውስጥ ጥብቅና ሚስጥራዊ ጉባኤ ተካሂዶ ነበር፤ መረጃ እንዳይወጣ ታፍኖ፥ መገናኛ ብዙሀን እንዳይሰሙ ተደርጎ ምርጫ ተከናውኗል፤ ስለ ጉዳዩ ከአንተ መስማታችን ነው ያሉኝ ጋዜጠኞችና ፌዴሬሽኖችም ነበሩ፤ መንግስታዊው የባህልና ስፖርት ሚንስቴር እንኳን በስፍራው አልተገኘም
ነገሮችን በስሌት በመበለት የተካኑት ብቸኛው እጩ ዶ/ር አሸብር ወ/ጊዮርጊስ የሀገሪቱ ህግ ባይፈቅድላቸውም ለሶስተኛ ጊዜ የኦሊምፒክ ኮሚቴ ፕሬዝዳንት ሆነው ተመርጠዋል፤ የያዙት ወንበር ገና አስር ወር ቢቀረውም ሌላ የስልጣን ዘመን ሸምተዋል፤ ሌሎች ተመራጮችም አሉ፥ ዝርዝሩን እነሆ፦
★ የምርጫ ቅድመ ዝግጅትና ሚስጥራዊነት
ከአስራ አምስት ቀናት በፊት በማሪዮት ሆቴል ለትናንቱ ጉባኤ ይረዳ ዘንድ የተመረጡ ተሳታፊዎችን የማሳመንና የደንብ ማሻሻያ ውይይት ተካሂዶ ነበር፤ በዋናነት ዶክተሩን ለሶስተኛ የስራ ዘመን ለማስመረጥ የማግባባት ስራ ተከናውኗል፤ ሌሎች ፌዴሬሽኖች ተወዳዳሪ እንዳያቀርቡና ዶ/ር አሸብር ብቸኛ እጩ እንዲሆኑ ከፍተኛ የማሳመን ጫና ተደርጓል፤ በተጨማሪ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን በቋሚነት የኦሊምፒክ ኮሚቴ ምክትል ፕሬዝዳንትነት ቦታን እንዲይዝ ደንብ ተሻሽሎ ፀድቋል፤ ፌዴሬሽኖች ለአመራርና ለስራ አስፈፃሚነት እጩ መላክ ቢኖርባቸውም አንዳንዶቹ አልደረሰንም ብለዋል፤ በተለምዶ እጩ ለመላክና ለመገምገም የአንድ ወር ጊዜ ቢሰጥም ገሚሱ ምርጫ መኖሩን ሳያውቅ ሌላው ተወካዩን ሳይልክ በአስራ አምስት ቀን ውስጥ ተጣድፎ ምርጫው ተከናውኗል፤ ትናንት የይስሙላ ምርጫ በጉባኤው ተደረገ እንጂ ሁሉም ነገር ያለቀው ከአስራ አምስት ቀናት በፊት ነበር ብለውኛል ምንጮቼ
እናም በትናንቱ ምርጫ ብቸኛው እጩ ዶ/ር አሸብር ወ/ጊዮርጊስ ለሶስተኛ የስራ ዘመን ኦሊምፒክ ኮሚቴን እንዲመሩ ተሹመዋል፤ ከስራቸው ደግሞ ሶስት ምክትሎች ተሰይመዋል፤ ከዚህ በፊትም ምክትል የነበሩት የቀድሞ አትሌቶቹ ሻለቃ ሀይሌ ገ/ስላሴና ኮማንደር ብርሀኔ አደሬ አሁንም በምክትልነት ፕሬዝዳንትነታቸው ቀጥለዋል፤ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን በቋሚነት የኦሊምፒክ ኮሚቴው ምክትል ይሆናል በሚለው አዲሱ ደንብ መሰረት ደግሞ ረዳት ኮሚሽነር ደራርቱ ቱሉ በምክትል ማዕረግ ተሹማለች፤ አቶ ዳዊት አስፋው በዋና ፀሀፊነት ዶ/ር ኤደን አሸናፊ በአቃቢተ ንዋይነት ልክ እንደቀደመው ሀላፊነታቸው አሁንም ቀጥለዋል
የትናንቱ ምርጫ በሚስጥር የተያዘ ለመገናኛ ብዙሀን ዝግ የሆነ ለብዙዎች ድንገቴ ነበር፤ የመንግስት አካል የሆነው የባህልና ስፖርት ሚንስቴር በሁሉም ምርጫዎች ላይ በታዛቢነት መገኘት ቢኖርበትም በትናንቱ የኦሊምፒክ ኮሚቴ ጉባኤ ላይ ግን አልነበረም፤ በተመሳሳይ የኦሊምፒክ ምርጫን ማከናወን ያለባቸው የኦሊምፒክ ስፖርቶች የሆኑ ፌዴሬሽኖች ቢሆኑም አንዳንዶቹ በጉባኤው እንዳልተገኙ ከተሳታፊዎቹ አረጋግጫለሁ፤ ለምሳሌ የትልቁ ተቋም የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ተወካይ አልተገኘም፤ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ግን ከተቋሙ የተወከለ አባሉን ልኳል፤ አንዳንዶቹ ደግሞ ይፋዊ ደብዳቤ እንዳልደረሳቸው ገልፀውልኛል፤ ስለ ጉባኤው በስልክ የቴሌግራም ግሩፕ መልዕክት የደረሳቸውም ነበሩ፤ ስብሰባው በተደረገበት ቦታ ደግሞ ጥብቅ ቁጥጥርና ጥበቃ ታይቷል፤ ምናልባት ባለፈው ምርጫ እንዳጋጠመው ወከባና የተቃውሞ ሰልፍ እንዳይኖር በመስጋት ሊሆን ይችላል ተብሏል
★ ጊዜውን ያልጠበቀው ምርጫ
ዶ/ር አሸብርና የቦርድ አባላቱ የስራ ዘመናቸው ገና አልተጠናቀቀም፤ በአወዛጋቢ ሁኔታ የተመረጡት መጋቢት 20/2013 ነበር፤ የአራት አመት የስልጣን ጊዜያቸው ሊያበቃ ገና አስር ወር ይቀረዋል፤ ለምን ታድያ አሁን የሚለው መልስ የሚፈልግ ጥያቄ ነው፤ ይህ መሰል ክስተት ግን የመጀመሪያ አይደለም፤ ከሶስት አመት በፊት አወዛጋቢ የነበረው ምርጫ ከቶኪዮ ኦሊምፒክ በኋላ መስከረም ላይ እንዲደረግ በጉባኤው ቢወሰንም ፕሬዝዳንቱ ከኦሊምፒኩ በፊት መጋቢት ላይ ምርጫ አካሂደው በድራማዊ ትዕይንት ስልጣናቸውን ማስቀጠላቸው ይታወሳል፤ ያኔ ቅድሚያ ባህርዳር ሲከለከሉ ወደ ሀዋሳ ሄደው ሀዋሳም በፀጥታ ሀይሎች ተሳደው አዲስ አበባ በኮሚቴው ፅህፈት ቤት በር ዘግተው ምርጫ ማከናወናቸውና 13 ማህበራት መቃወማቸው ብሎም ፕሬዝዳንቱ ለእስር መዳረጋቸው ይታወሳል፤ አሁን ደግሞ በፓሪስ ኦሊምፒክ ዋዜማ ላይ በድንገቴ ምርጫ ዙፋናቸውን አስቀጥለዋል
★ ቤተኛ ተመራጮችና ጥያቄ የሚያስነሱ አባላት
ስልጣኑን ባላጠናቀቀው የኦሊምፒክ ኮሚቴ አመራር ውስጥ የሚገኙ አብዛኞቹ አመራሮችና የቦርድ አባላት በድጋሚ ለቀጣዩ አራት አመታት ኦሊምፒክ ኮሚቴውን እንዲያገለግሉ ተመርጠዋል፤ ከሀያዎቹ የቦርድ አባላት መካከል አስራ አራቱ ነባር ቤተኛ ናቸው፤ ከነባሮቹ መካከል አሁንም በምክትል ፕሬዝዳንትነት እንዲቀጥል የተሾመው ሻለቃ ሀይሌ ገ/ስላሴ በኦሊምፒክ ኮሚቴው እንቅስቃሴ ውስጥ ንቁ ተሳትፎ አድርጎ አያውቅም፤ በስብሰባዎችና በጉባኤ ላይም አይገኝም፤ አሁንም ግን ድጋሚ ተመርጧል፤ አዲስ ከገቡት መካከልም ጥያቄ የሚነሳባቸው አባላትና ማህበራት አሉ፤ ለምሳሌ የኦሊምፒክ ስፖርት ያልሆነው የባህል ስፖርቶች ፌዴሬሽን የኦሊምፒክ ኮሚቴ የቦርድ አባል ሆኖ መካተቱ አስገራሚ ሆኗል፤ በሌላ በኩል ከኦሊምፒክ እኩል አቻ የሆነው ፓራ ኦሊምፒክ በተመሳሳይ መካተቱ ጥያቄ የሚያስነሳ ነው፤ አራት አትሌቶች፣ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን፣ ፓራ ኦሊምፒክ፣ ክልሎችና የአለም አቀፉ ኦሊምፒክ ተወካይ ያለ ምርጫ በቀጥታ የቦርድ አባላት ሆነዋል
★ የተጣሱት የሀገሪቱ ህጎች
አንድ፦ የሀገሪቱ የስፖርት ማህበራት ህግ እንደሚለው አንድ ስራ አስፈፃሚ ለሁለት የስራ ዘመን ወይም ለስምንት አመት ብቻ ማገልገል አለበት፤ ለሶስተኛ ጊዜ መወዳደርም መመረጥም አይችልም፤ በአጭሩ የስልጣን ዘመኑ ስምንት አመት ብቻ ነው፤ ይህ ህግ ለሁሉም የስፖርት ፌዴሬሽኖችና ማህበራት የሚውል ነው። የኦሊምፒክ ኮሚቴው አለቃ ግን ይህንን ህግ ጥሰው ለሶስተኛ የስራ ዘመን ትናንት በሚስጥር ተመርጠዋል፤ የገዢው ፓርቲና የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባሉ ዶ/ር አሸብር እኛ የአለም አቀፉ የኦሊምፒክ ኮሚቴ ህግ እንጂ የሀገሪቱ መንግስት የሚያወጣው ህግ አይገዛንም የሚል አቋም ይዘው ግዙፉን ተቋም እስከ አስራ ሁለተኛ አመታቸው ለመምራት ተዘጋጅተዋል፤ በዚህም ህጉን ሽረው ተሹመው ሌሎቹን ሹመዋል፤ ይህ ክስተት በሌሎች ፌዴሬሽኖች ላይም እንዳይዛመት ያስፈራል፤ በሁለተኛ የስልጣን ዘመናቸው ላይ የሚገኙት የእግርኳስና አትሌቲክስ ፌዴሬሽን አመራሮች ለሶስተኛ ዙር ምርጫ ሊወዳደሩ ይችላሉ የሚል ስጋት አለ፤ ስለሆነም ህጉን ማስከበር አልያም ማሻሻል ተገቢ ነው
ሁለት፦ የክልል ስፖርት ኮሚሽን ኮሚሽነሮችና የፌዴሬሽን የፅህፈት ቤት ሀላፊዎች በማህበራት ጉባኤዎች ላይ መመረጥና በድምፅ መሳተፍ እንደማይችሉ ገለልተኛ ሆነው ብቻ እንዲሳተፉ የስፖርት ማህበራት ህጉ ይደነግጋል፤ አሁን ግን የክልል ኦሊምፒክ ቅርንጫፎች በሚል በቦርድ አባልነት ገብተዋል፤ የአዲስ አበባ አስተዳደር እንዲሁም የሀረሪና የአማራ ስፖርት ኮሚሽኖች የኦሊምፒክ ኮሚቴ የቦርድ አባል ሆነው ተመርጠዋል፤ መንግስታዊ ተቋማትን በማስገባት ይህም ህግ ተሽሯል
ሶስት፦ ኢትዮጵያዊ ዜግነት የሌላቸው በማህበራት አመራርነት መመረጥ እንደማይችሉ በዚሁ የስፖርት ማህበራት ህግ ላይ ተቀምጧል፤ ሁለቱ ትውልደ ኢትዮጵያዊያን አሜሪካዊው አቶ ዳዊት አስፋው በዋና ፀሀፊነት እንግሊዛዊቷ ዶ/ር ኤደን አሸናፊ ደግሞ በአቃቢተ ነዋይነት በድጋሚ ተመርጠው ህጉ ፋይዳ እንደሌለው አሳይተዋል
አራት፦ የኦሊምፒክ ስፖርት ያልሆኑ ማህበራት በኢትዮጵያ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ውስጥ ድምፅ ሰጪ ተመራጭ አባል ወይም መሪ ሆነው መስራት እንደማይችሉ ሀገራዊው ህግ ያዛል፤ ትናንት ግን ከኦሊምፒክ ጋር ምንም ግንኙነት የሌለው የባህል ስፖርቶች ተመርጧል
★ እነማን ተመረጡ?
አንድ ፕሬዝዳንት፣ ሶስት ምክትል ፕሬዝዳንቶች፣ አንድ ዋና ፀሀፊ፣ አንድ አቃቢተ ንዋይ፣ 13 የቦርድ አባላት፣ አራት አትሌቶች፣ ሁለት ፌዴሬሽኖችና ሁለት ክልሎች በትናንቱ የኦሊምፒክ ኮሚቴ ጉባኤ ተሰይመዋል፤ በተጨማሪ በአለም አቀፉ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ውስጥ በከፍተኛ ሀላፊነት ላይ የሚገኙት ወ/ሮ ዳግማዊት ፀሀዬ በድጋሚ ተካተዋል፤ እንደ ሀይሌ ሁሉ ወ/ሮ ዳግማዊትም በዶ/ር አሸብር ካቢኔ ውስጥ ብዙም ተሳትፎ የሌላቸው እንደውም በግፍ የተገፉ ሙያተኛ ናቸው
ሙሉ ተመራጮቹን እነሆ፦
1 ዶ/ር አሸብር ወ/ጊዮርጊስ.. ከቅርጫት ኳስ... ፕሬዝዳንት.
2 ረዳትኮሚሽነር ደራርቱ ቱሉ..ከአትሌቲክስ..ምክትል ፕሬዝዳንት
3 ሻለቃ ሀይሌ ገ/ስላሴ...አትሌት...ምክትል ፕሬዝዳንት
4 ኮማንደር ብርሀኔ አደሬ...አትሌት...ምክትል ፕሬዝዳንት
5 አቶ ዳዊት አስፋው...ከቴኳንዶ...ዋና ፀሀፊ
6 ዶ/ር ኤደን አሸናፊ... ከብስክሌት...አቃቢተ ንዋይ
7 ዶ/ር ግዮን ሰይፉ...ከፓራ ኦሊምፒክ...የቦርድ አባል
8 ዶ/ር ፍትህ ወልደሰንበት...ከእጅ ኳስ...የቦርድ አባል
9 አቶ ኢትዮጵያ በዴቻ...ከካራቴ...የቦርድ አባል
10 አቶ መስፍን አበራ...ከቮሊቦል...የቦርድ አባል
11 አቶ ጥላሁን ታደሰ... ከክብደት ማንሳት...የቦርድ አባል
12 አቶ ሲሳይ ዮሀንስ...ከጠረጴዛ ቴኒስ...የቦርድ አባል
13 ወ/ሮ ህይወት መሀመድ..ከባህል ስፖርት..የቦርድ አባል
14 አቶ ሚንልክ ሀብቱ...ከቦውሊንግ...የቦርድ አባል
15 አትሌት ቀነኒሳ በቀለ....አትሌት...የቦርድ አባል
16 አትሌት ጉዳፍ ፀጋዬ...አትሌት...የቦርድ አባል
17 አዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር....የቦርድ አባል
18 ሀረሪ ክልል...የቦርድ አባል
19 አቶ ባዘዘው ጫኔ...ከአማራ...የቦርድ አባል
20 ወ/ሮ ዳግማዊት ፀሀዬ...ከአለም አቀፉ ኦሊምፒክ ኮሚቴ...የቦርድ አባል ሆነዋል
★ ጥያቄዎች?
የትናንቱ ጉባኤ ለምን በዝግና በሚስጥር ተካሄደ? አንዱን ፌዴሬሽን በመጥራት ሌላውን በመዝለል ለምን ተከናወነ? የምርጫው ጊዜ ሳይደርስ ለምን ምርጫ ተካሄደ? ከአንድም አራት የስፖርት ማህበራት ህጎች ሲሻሩ ለምን ዝምታን ተመረጠ? እግርኳስ ፌዴሬሽን ለምን ተወካይ አላከም? ለምን የቦርድ አባልነት ውስጥ አልገባም? ከሶስት አመት በፊት ምርጫ ሲካሄድ ህገወጥ ነው ብሎ ሰልፍ የወጣው አትሌቲክስ ፌዴሬሽን አሁን ተመሳሳይ ነገር ሲፈፀም ለምን ዝምታን መረጠ? ባህልና ስፖርት ሚንስቴርስ ለምን ጉዳዩን ችላ አለው? እኮ ለምን?
via(ታምሩ ዓለሙ)